ጠብቀውና ላልተው የሚነበቡ ቃላት ሲጻፉ የሚ(ል)ለዩበት፣
ድምጽን ከጽሑፍ ጋር ለማጣጣም ሳድስን መደበል እንደ አማራጭ መፍትሔነት የቀረበበት
በአማርኛ መጻፍ እያዘወተርኩ ስመጣ ተደጋግሞ እየገጠመኝ ያለውን የ “ማጥበቅና ማላላት” ንባብ የሚሹ ቃላትን አስመልክቶ የሚፈጠረውን ችግርና መፍትሔም ሊሆን ይችላል ያልኩትን በምክረ ሀሳቦች ማዳበር አስፈላጊ ሆኖ ታየኝ። እኔ በማሕበራዊ ሚዲያ በማግጋራቸው (በማግጋራቸው) አንዳንድ ጽሑፎች ላይም መጠቀም ከጀመርኩ ቆየሁ። ሌሎች ወገኖች ይህን ያደርጉ እንደሆነ እርግጠኛ አይደለሁም። ቢኖሩም በየግላችን የምንከተለው አካሄድ እውቅና ተሰጥቶት በሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ካልተካተተ ከመፍትሔነት ይልቅ ግራ ማጋባትን ያስከትላል። በዚሁ የማጥበቅና የማላላት ንባብ ምክንያትም አማርኛ በአገራችን ላሉ ብዙ ቋንቋዎች መጠቀሚያነት እንዳይውል ሲፈራ (ሲፍፈራ) ቆይቷል። በመሆኑም ሀሳቦች ተንሸራሽረው ወጥነት ያለው አካሄድ እንዲፈጠር ማድረግ አስፈላጊ ነው ብዬ አምናለሁ። ለምሳሌ “አለ” እና “አለ” መካከል በጽሑፍነት ሲቀመጡ ምንም ልዩነት አናይባቸውም። በድምጽ ሲነገሩ ግን ጠብቀው “አልለ” እና ላልቶ “አለ” መባሉ የታወቀ ነውና ይህንኑ ለምን በጽሑፍ የሚወከልበትን መንገድ አንፈልግም ብዬ ነው። በእኔ አስተያየት ጠበቅ ብሎ የሚነበበውን ከሚላላው ለመለየት ሳድስ ፊደል በመጨመር “አልለ” ብንለው “ል”ቃሉን ስንናገር በንባብ ጊዜ ላንቃችን ውስጥ የሚፈጠረውን ድምጽ የሚተካ ፊደል በመሆኑ ንግግርን ከጽሑፍ ጋር ያጣጣመ መፍትሔ ሆኖ ይታየኛል። እንዲህ ዓይነት ችግሮችን በዐውድ እንለያቸዋለን ቢባል እንኳ ይህ ንባብን የሚጎትትና “የትኛውን ለማለት ይሆን?” የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ሌላ ሥራ የሚፈጥር ነው። ስለዚህ በቀላሉ አጥብቆ ለማንበብ የሚያግዝ የተከታዩን ቃል ሳድስ ፊደል በማስቀደም በቀላሉ እንዲጠብቅ ማድረግ ሲቻል (ሲችቻል) አይቻለሁ።
በተግባር ከገጠሙኝ ንባቦች መካከልም አንዳንድ ምሳሌዎችን መጨመር ችግሩን የበለጠ ሊያሳይልን ይችላል። “ሲገባ” የሚለው ቃል የመውጣት ተቃራኒ የሆነውን “መግባት” የሚያመለክተው “ገ” ላልቶ ሲነበብ ነው። ተገቢ ነው የሚል ፍቺ እንዲሰጠን ከፈለግን ግን “ገ” ን አጥብቀን ማንበብ አለብን። “ገ” የላላችው ብቻዋን በመሆኗ ነውና “ግ” ከጎኗ እንድትሆን ብናደርግላት “ሲግገባ” ተብሎ ይጻፍና ጠብቆ ሲነበብ በላንቃችንው ውስጥ የሚፈጠረው ድምጽም በ “ግ” እገዛ ተፈጥሮ ንባብም ንግግርም በአንድ ተስማምተው መፍትሔ መጣልን ማለት ነው። ከዚሁ ቃል ጋር በተገናኘ በየሳምንቱ እሁድ ወይም የጌታ እራት ሥርዓት በቤተክርስቲያን በሚካሄድበት ጊዜ በ1ቆሮ.11፥27፣29 ላይ ያለው “ሳይገባው” የሚለው ቃል ጠብቆም ላልቶም እየተነበበ ሰባኪውም ሥርዓት አስፈጻሚውንም፣ ምዕመናንም ሲቸገሩበት ይስተዋላል። በእንግሊዝኛ unworthily ወይም በእናት ቋንቋው “ἀναξίως” አናክሲዮስ ወደሚለው ሄደው ማረጋገጥ የሚችሉ ደግሞ ብዙዎች ስላልሆኑ በማስተማርም፣ በመስበክም፣ በማንበብም ጊዜ ግራ መጋባትን እያስከተለ ይገኛል። የአማርኛው ትርጉም “ሳይ(ግ)ገባው” የሚል ፈጠን ተብሎና አጥብቆ የማስነበብ አማራጭ ቢኖረው ኖሮ ይህ ችግር ተወግዶ ነበር። ይህን በትርጉም ሊፈታ የሚችል ምሳሌ አድርጌ ሳቀርብ ተርጓሚዎቹ የመረጡን እና ቃሉ ማለትም “unworthily” ን የጌታ እራት የሚወስደውን ሰው አመልካች (ቅጽል) እንዲሆን የወሰኑትን ውሳኔ እንደነበረ ወስጄ ነው። ሳይግገባው ወይም “anaxios” የሚለው ቃል ድርጊቱን ወይስ አድራጊውን የሚገልጥ ነው የሚለውን ሌላ ክርክር (ካነሳሁት የአማርኛ ንባብ ጉዳይ ጋር ስለማይገናኝ) የሲህ መወያያ ዐሳብ አካል እንዳልሆነ እግረ መንገዴን ጠቆም ማድረግ እወዳለሁ። በዚህ የተዛነፈ ንባብ ምክንያትም “ገብቶት፣ ተረድቶ፣ ተምሮ፣ አውቆ...” ነው የጌታን እራት መውሰድ ያለበት የሚል እና የማይገባው ሳይሆን የማይ(ግ)ገባው ሰው እንዳይወስድ የሚል ክርክር እንዲፈጠር አድርጓል። ከላይ ጠቆም እንዳደረግኋችሁ፣ እኔ ክርክሩ አልገባውም (አላወቀም፣ አልተረዳም) ወይም አልተገባውም (በልዩ ልዩ ምክንያቶች) ብለን ከምንሟገትበት የሥርዓቱ ተካፋይ ሰው ማንነት ይልቅ፣ ግሱን የሚገልጥ (ተውሳኬ ግስ) ሆኖ ተተርጉሞ ውዝግቡ የአወሳሰዱን ሁኔታ እንዲያመለክት መሆን አለበት ማለቴ ሌላ ርዕሰ ጉዳይ ቢሆንም ጉዳዩን ለማጥራት እዚህ ጋ ደግሜ መጠቆም እንዳለብኝ ፈልጊያለሁ።
እንግዲህ የዛሬው መልዕክቴ፣ ከላይ እንዳየነው አነባበብ (በተቻለ መጠን) በአጻጻፍ ተደግፎ መልዕክትን ማጥራት አለበት በሚለው መርህ እና ይህን የሚያሳልጥ ወጥ አካሄድ አለመኖሩ ይታወቃል። በዚህም ምክንያት የተፈጠረውንም ችግር ለመፍታት የቀረበውን ይህን የቀዳሚውን “ጠብቆ ተነባቢ” ፊደል የሚከተል አምሳያ “አስጠባቂ የሚሆን” ሳድስ ፊደል በመደበል ጽሑፍን ከንግግር ጋር ብናስማማ ምን ይመስላችኋል የሚለውን ሀሳብ ለማጋራት ነው።ይህን የምታነቡ (የምታነብቡ) ሁሉ በዚህ ሁኔታ መጻፍ (መጽጻፍ) ሲችሉ የተሻለ መትሔ ሊገኝላቸው የሚችሉትን የገጠሟችሁን ቃላት ከጥቂት ማብራሪያ ጋር ብታጋሩ እና በተለይም እንደ ጌታ እራቱ ዓይነት ተግባራዊ ችግር የፈጠሩበትን ሁኔታ በማጋራት ችግሩ መፍትሔ የሚሻ ዋና ጉዳይ እንጂ ትንሽ እንዳልሆነ እንድናውቅ ታግዙን ዘንድ እጋብዛለሁ።
ሰላም ይሁን!

አንተ “ጠብቀውና ላልተው” ያልካቸው የአድራጊና የተደራጊ ግሦች ጉዳይ ዐዲስ አለማየሁ በሚጠብቀው ቀለም ላይ ነቁጥ በማኖር ችግሩን እንድንፈታ መፍትሔ አቅርበው ነበር (በ”ፍቅር እስከ መቃብር” መጽሐፋቸው መግቢያ ላይ)። ልዩነቱ አንተ ማጥበቁን በሆሄ እንግለጽ ስትል እሳቸው በትእምርት (በነቁጥ) ማለታቸው ብቻ ነው!
ተሰሚ (ተደማጭ) የሆነ የቋንቋ ማዕከል ከሌለ የግል ጥረት ሥር የሚሰድ አይመስለኝም! ግና ሠናይ ውእቱ መሆኑን በአድናቆት እገልጻለሁ!